ኢትዮጵያ ቡና የሚለውን ስያሜ ከመያዙ በፊት ወንድማማቾች፣ የንጋት ኮከብ፣ ኢትዮጵያ ቡና ኮርፖሬሽን አሁን ደግሞ ኢትዮጵያ ቡና የሚል ስም ይዞ ቀጥሏል …የ48 አመት ታሪክ ካለው ኢትዮጵያ ቡና በመቀጠል ከ41 አመታት በላይ በክለቡ አመራርነት ስማቸው የሚጠራው መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞ ናቸው …. ጠንካራ የስራ ሰው በእግርኳሱ ከሚደመጡ አመራሮች መሃል አንዱና ዋናው መቶ አለቃ መሆናቸው ብዙዎችን ያስማማል። የቀድሞ የአየር ሃይል ባልደረባ የሆኑት መቶ አለቃ ፈቃቸ ማሞ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበርና የሚወዱትን ክለባቸው ኢትዮጵያ ቡናን በቦርድ ሰብሳቢነት እየመሩ ይገኛሉ…. ከሊጉ ዮሴፍ ከፈለኝ ጋር ቆይታ ያደረጉት መቶ አለቃ ፈቃደ… መመሪያው ይተገበራል ወይም ሊጉ ይፈርሳል ስለማለታቸው፣ ስለ ሊጉ የተጨዋቾች የዝውውር ዋጋ ከመጋረጃ ጀርባና ፊት መካሄዱ መቀጠሉን፣ ሊጉ ጥርስ አለው። ስለማለታቸው በቀጣይስ አምስት አመታት ኢትዮጵያ ቡና የሁሉም የበላይ ይሆናል ያሉበትን፣ በዲ ኤስ ቲቪ ዙሪያ ስላለው ፍርሃት፣ ስለ አዲሱ የዝውውር ተቆጣጣሪ ኮሚቴ፣ ዝውውር ላይ ስለሚከተሉት ፖሊሲና መሰል ጉዳዮች ዙሪያ ለተነሳላቸው ጥያቄዎች ጠንካራ ምላሽ ሰጥተዋል….
ሊግ:- መቶ አለቃ አመሰግናለሁ… በርዎ ክፍት ስለሆነና ለቃለምልልሱ ፍቃደኛ ስለሆኑም ደግሜ አመሰግናለሁ
ፈቃደ:– እኔም አመሰግናለሁ በሬ ሁሌም ክፍት ነው እውነተኛ ዜና ለሚያስተላልፉ ሚዲያዎችጰ ሁሉ በሬ ክፍት ነው
ሊግ:- አመሰግናለሁ በድጋሚ እንደ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አመቱ እንዴት አለፈ..?
ፈቃደ:– በሊጉ ዘርፈ ብዙ ነገሮች አሉ አንዱ እግርኳስ ነው በሜዳ ተገኝተን እንደሚያወዳድር አካል ባለፉት 4 አመታት ያልተፈታ ችግር አለ.. እሱም የከተማና የሜዳ ችግር ነው..የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ተንከራታች ነው አዳማ ድሬዳዋ ሀዋሳ እያልን ጨረሴን የሀዋሳውን አዲስ አበባ ላይ ለመጨረስ አስበን አልተሳካልንም በግራም በቀኝም ብንለው አዲስ አበባ ላይ ማካሄድ አልቻልንም ስደቱ ቀጥሎ ሀዋሳ ላይ ጨረስን ..ከውድድር አንጻር እንደ አጠቃላይ ክለቦቻችን የመለማመጃ ሜዳ ችግር የግጥሚያው አዲስ አበባ ወደ መዲናዋ አለመመለሳችን ካልሆነ በስተቀር ሌላው በጥሩ ሁኔታ ጨርሰናል…
ውድድር ስንል ደግሞ ዳኝነቱ ቡድኖቹ ሰአቱን ጠብቀው ለውድድሩ መቅረብ በዲሲፕሊን ውድድሮቹን በማካሄድ አመቱ ተሳክቶልናል ማለት ይቻላል…
ሊግ:– 2017 ከዲ ኤስ ቲቪ ጋር ያለው ውል የመጨረሻው አምስተኛ አመት ይሞላል… ስለመቀጠሉ ያሰጋናል..?
ፈቃደ:- በጣም… በጣም ነው የሚያሰጋን…. የሚያሰጋን ምክንያቶች ደግሞ አሉ… የመጀመሪያ ዲ ኤስ ቲቪ ሲመጣ የኢትዮጵያ ህዝብ ወደ 130 ሚሊዮን ነው ይህ ህዝብ እግርኳስ ወዳድ ነው እዚህ ብገባ ጥሩ ቢዝነስ እስራለሁ ብሎ ለትርፍ ነው የገባው….ባለፉት አመታት ግን ገጠመኝ ያለው ትርፍ ሳይሆን ኪሳራ ነው ሌሎች ምክንያቶች ቢኖሩትም…. የዲ ኤስ ቲቪን ዲኮደር የሚሸጠው መልቲቾይስ ኢትዮጵያ ነው…ከመልቲ ቾይዝ የዲኮደሩ ሽያጭ ሂደት ጋር ተያይዞ በራሱ የሚገመገም ቢሆንም ዲ ኤስ ቲቪ ግን ኪሳራ ገጥሞኛል ብሎ ነበር እኛ ደግም አይ አልገጠመህም ብለን ክርክር ገጥመናል ዞሮ ዞሮ የሚናገረው ሂሳቡ ነውና ቀጣይ ውል ማራዘም ላይ ስጋት አለን። ሌላኛው ያው እንደሚታወቀው ዲ ኤስ ቲቪና ሱገር ስፖርት የተለያዩ ናቸው ሌላ ድርጅት እነሱን ለመግዛት ሂሳብ አቅርቧል ለሁለቱም የቀረበው ሂሳብ ትክክለኛ ነው የሚለው በደቡብ አፍሪካ ህግ መሰረት የሀገሪቱ ፓርላማ አይቶት ዋጋው ትክክል ነው ካለ ሽያጩ ይከናወናል ተብሎ ነው የሚጠበቀውና እዛም ሰፈር ከፍተኛ ችግር አለ ከሁለቱ ጋር ተያይዞ ያሰጋናል።
ሊግ:- አዲሱ የበጀት ደንቡ ተቀባይነቱ ላይ ችግር ገጥሞታል የሚሉ ወገኖች አሉ…እናንተስ እኔዴት ገመገማችሁት..?
ፈቃደ:- በሁለት መንገድ እንየው …በጭምጭምታ ደረጃ የሰማነው መረጃ አለ ..ያን ተንተርሰን ችግሩን ፈጥረዋል የተባሉትን ክለቦች ጠርተን እያነጋገርን ነው.. በጣም መሰመር ያለበት ግን የጠረጠርነው ነገር በመረጃ ተደግፎ ካገኘነው እውነት ከሆነ ችግር የሚገጥመው ክለቦቹንና ተጨዋቾቹን እንጂ ሊጉን አይደለም.. ያልሆነ ነገር ከተሰራ ወንጀል ነው ፍርድ ቤት ሳይኬድ በተቀመጠው ደንብ መሰረት እገዳ ይኖራል ርምጃው ይከፋል ችግሩ ለክለቦቹና ለተጨዋቾቹ ነው ጠርተን ለማስጠንቀቅ ሞክረናል ህግ ከጣሰ የተቀመጡ ድንጋጌዎች አሉ መተግበሩ የግድ ነው
ሊግ:- ማስረጃ ላይገኝ ይችላል የህሊናና የሞራል እይታዎችስ ውሳኔ እንዲሰጥበት አያደርጉም..? ለምሳሌ የደመወዝ መጠን ቀንሶ ለሌላ ክለብ መፈረምን የመሰለ ነገርስ ከግምት አይገባም..?
ፈቃደ:– ቁጭ ብለው ለሚመረምሩ ሰዎች እንተወው አስቀድመን ፍርድ አንስጥ እኔም ፍርድ አልሰጥም.. አንዳንድ ተጨባጭ ማስረጃዎች ሊጉ ጋር ደርሰዋል ..
ምን ውጤት ያመጣሉ የሚለው የተቋቋመው ኮሚቴ ቁጭ ብሎ የሚያየው ነው የሚሆነው… ተጨማሪ መረጃ ያስፈልገዋል አያስፈልገውም የሚለውን በቀጣይ የሚወስን ነው የሚሆነው… ለጊዜው ይሄ ነው ያለው
ሊግ:- የተቋቋመው አዲሱ ኮሚቴ ስራ ጀመረ እንዴ ምኑም አይሰማም..?
ፈቃደ:– ደንቡን አርቅቀን ከጨረስን በኋላ የሄድነው ኮሚቴውን ማቋቋም ነበር እያቋቋምን እያለ ግን የዝውውር መስኮቱ ተከፈተ..ሀምል 8 የዝውውር መስኮት ሲከፈት የሰማናቸው ጭምምታዎች አብረው ተከሰቱ የመደራረብና የመሽቀዳደም ሁኔታ እንደ ችግር ተከሰተ ለኮሚቴው መመሪያው ተልኮለታል ገና ደግሞ የስራ ክፍፍል ያደርጋል ኮሚቴው ስራውን ይቀጥላል ችግር የለውም። እዚህ ላይ የምናገረው ግን አሜሪካም ይሁን ኢትዮጵያ ወንጀልና ፍትህ እኩል አይሄድም ሁልጊዜ ወንጀል ይቀድማል.. የፍትህ አካሉ። ደግሞ ወንጀሉን የሚመጥን ፍትህ ላይኖር ይችላል.. ይህን ተረዱን ..ነገር ግን ተከታትሎ ወንጀሉን አጋልጦ ርምጃ ይወሰዳል አይቀርም …ሌላ ወንጀለኛ ደግሞ በአዲስ መልክ በወንጀል ቀድሞ ይሄዳል….ወንጀልና ፍትህ እኩል እንደማይሄዱ ተረዱን .. መጠየቅ ያለበት ወንጀሉ እንደተፈጸመ የፍትህ አካሉ በምን ፍጥነት ተከተለው የሚለው ነው አበቃ።
ሊግ:- ሌሎች ክለቦችስ ይህን ክፍተት እየተጠቀሙበት ቢሆንስ..?
ፈቃደ:– በክለብ ስም ብዬ ለመናገር እቸገራለሁ ነገር ግን ሃላፊዎቹ ክለቡን ለመጥቀም ነው ራሳቸውን ለመጥቀም ነው ግራ ይገባል… አካሄዱ ልክ እንዳልሆነ ሲነገራቸው የሚቀልዱ በቧልት የሚመልሱ አሉ። ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ሲነገራቸው ምላሻቸው ቧልትና ፌዝ ነው አመራሮቹ ደንገጥ ብለው ይሄ ነገር ከኔ አልፎ ክለቤንም የሚያስቀጣ ነው ለካ ይሄማ የክልሉ መንግስትና ደጋፊዎቹ ይጠይቁኛል የሚል ሀሳብ የለውም ይሄ ደግሞ ተገቢ አይደለም ብነካ የክልሉ መንግስት ይከላከልልኛል ብለው የሚያስቡ ይመስለኛል ይሄ ተገቢ አይደለም .. እንዴት አድርጎ እንደሚከላከልላቸው አልገባኝም ተፈጸመ የተባለው ወንጀል እውነት ከሆነ አንድ ክልል ሌብነትና ወንጀልን እንዴት እንደሚሞግትለት አይገባኝም በግሌ ክልሉ እንደማይሞግትለት ነው የማምነው.. እስኪያዙ ነው የሚፎክሩት ለማንኛውም ይሄን ማረም አለባቸው ብዬ ነው የምመክረው።
ሊግ:- ለገንዘብ ክፍፍሉና ለሚሠጣው ገንዘብ ትልቅ ጥንቃቄ የማድረግ ክፍተት ያለ ይመስላል..?
ፈቃደ:- ሲጀመር ያለውን እኩል እናከፋፍል ነበር በኋላ ግነሰ ለምን በውጤት በደረጃ አናረገውም ብለን በሜሪት ክፍያውን አበላልጠን መስጠት ጀመርን ነገር ግን ገንዘቡን ሳይሆን የሚያዩት የመውጣትና የመውረዱን ብቻ ነው ፋይናንሱን አላዩትም.ነበር በኔ ክለብ በኢትዮጵያ ቡና የደረሰ አንድ ጥሩ ምሳሌ ልንገርህ …የመጨረሻ ጨዋታ የተጫወትነው ከሀድያ ሆሳዕና ጋር ነበር ..
ከጨዋታው በፊት ተሸንፈን 3ኛነታችን ብንለቅና አራተኛ ብንሆን 1ሚሊዮን ብር ነው የምናጣው ተጠንቀቁና ተጫወቱ አልናቸው … ግን አልሆነም ተሸነፍን … ዕድል ሆነና በቀጣዩ ቀን ባህርዳር ከተማ ተሸነፎ 3ኛነታችንን ሳንለቅ ቀረን 1 ሚሊዮኑም ተረፈ ..እናም ክለቦቻችን ለገንዘቡ አያስቡም እኛ እንደምንጨነቀው አያስቡም ይሄ ከባድ ክፍተት ነው.. ለነገሩ አንድ ክለብ በፕሪሚየር ሊግ ደረጃ ደመወዝ ሆቴል ትራንስፖርት አበል ደምረን ስናይ ከ1ሚሊይን ብር ያወጣል ይህን ካሰበ ገቢው ላይ ማተኮር አለበት ብዬ አስባለሁ …እንደሚዲያ እንደኛም ክለቦቹ ነገ ምን ይፈጠር ብለው ቀድመው አስበው መዘጋጀት ላይ ክፍተት አለ..
ሊግ:- የዛሬ 6 አመት ዋንጫውን ሆቴል ውስጥ የረሳ ክለብ ከዚያ አይነት አሳዛኝ ክስተት ወጥቶሊጉ አሁን ዋጋ ኖሮት ገቢ ተገኝቶበት እንደማየታችን ምን ስሜት ይሰማዎታል..?
ፈቃደ:- ይሄኮ የሰራንበት ነው ለፕሪሚየር ሊጉ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽንምኮ ሰርተናል ብዙ አሰራሮችን ለፌዴሬሽኑ አሳይተናል። የከፍተኛ ሊግና የአንደኛ ሊጉን ፎርማት ቀይሯል ይሄ እንደ ሀገር የመጣ ለውጥ ነው…ሁለት አይነት ማሊያ አድርጎ የሚገባ ቡድን ነበር አሁን አይታሰብም ይቀጣል እሱ ብቻ ሳይሆን ሰአት አክብሮ መገኘትን ለምደዋል ካልሆነ ይቀጣሉዋ የማይታዩ ግን ሊጋችን እያደገ እንደሆነ የሚያሳዩ ብዙ ለውጦች አሉ ይበልጥ ደግሞ ጨዋታዎቹ አዲስ አበባ ላይ ቢታዩ በይበልጥ ደስታችን ሙሉ በሆነ ነበር..
ሊግ:– አዲስ አበባ ላይ ላለመካሄዱ ትክክለኛ ምክንያቱን በደንብ መረመራችሁ ..?
ፈቃደ:– ከደህንነት አንጻር ብዙ ሰው ይፈራል ..አሁንኮ ካለን ቴክኖሎጂ አንጻር ስታዲየም ውስጥ 50ሺህ ሰው ቢገባ ማን ምን አለ ስንቴ ሳቀ የሚለውን ቆጥረን ማወቅ እንችላለንና ለመንግስት መግለጽ የምፈልገው ከደህንነት አንጻር የሚያሰጋን ነገር አለ ብዬ አላምንም የሚሳደበውን ዋልጌውን ልናወጣ ስለምንችል ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይቀርም እንደሚባለው ዋልጌው ተፈርቶ ኳሱ መቆም የለበትም …በግልጽ የምናገረው ተወልጄ ያደኩት አዲስ አበባ ነው። ጓደኞቼን ለማግኘት ብፈልግ ሲኒማ ቤት፣ ቲያትር ቤት ፣ ቤ/ክ፣ ወይም የፈለኩበት ቦታ ቢራ እየጠጣሁ እየተዝናናሁ እነኚህ ሁሉ የመፈጸም የእረፍት ቀን መብቴ ነው ስታዲየምም መግባት መብት ነው ለምንድነው የምትከለከለው.. ? መንግስት ለህብረተሰቡ ኳስ ሜዳዎችን ሊያዘጋጅልን ይገባል እንጂ ሊከለክል አይገባም የመዝናኛው ኢንዱስትሪ መብት ነው ሁለተኛ የትም ሀገር ቢኬድ ከፍተኛ ገቢ ለመንግስት የሚያስገኘው የመዝናኛው ኢንዱስትሪው ነው.. ይህን ኢንዱስቴሪ በግራ በቀኝ እየተኮረኮመ እስከመቼ ሊዘልቅ ነው ..? መለመድ አለበት ክቡር ጠቅላይ ሚኒስተሩ የአፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት አለብን አሉ እውነታቸውን ነው። አዲስ አበባ አምራለች እንኳን የአፍሪካ ዋንጫ የአለም ዋንጫ የማዘጋጀት የከተማ ውበት አላት የሚቀራት ግን ሰታዲየሞቾቿ እኩል መዋብ አለባቸው። ህዝቡን ወደ ስታዲየሙ መልሶ እየተቆጣጠርን ለምንድነው የማንሄደው ብዬ መንግስትን መጠየቅ እፈልጋለሁ…መንግስት ይህን በደንብ ማየት አለበት ብዬም አምናለሁ…
ሊግ:- ህጉ ይተገበራል ወይም ሊጉ ይፈርሳል… ይሄ አቋም እንደጸና ነው….?
ፈቃደ:– ተው ተው ..ቦርዱ ላይ ተወቅሼበታለሁ.. እንዴት ሊጉ ይፈርሳል ትላለህ ብለው ቅሬታቸውን ነግረውኛል…
ሊጉን የማፍረስ መብትስ የማነው ብለው ጠይቀውኛል ህግ ማክበርና ሊግ ማፍረስ አብረው የሚሄዱ አይሄዱም ሊጉ ይቆያል ህግን የሚጥሱ ክለቦችና ሰዎች ይቀጣሉ በሚለው ይቀየርልኝ / ሳቅ / ተጋነነ እንጂጠ ማንም መጥቶ የፈለገውን አድርጎ ወደ ቤቱ መሄድ አይችልም ለማለት ነው ትንሽ ተጋነነና አነጋጋሪ አደረገው….
ሊግ:– መቶ አለቃ እውነት አክሲዮን ማህበሩ የሚሉኝን ያህል ጥርስ አለው ..?
ፈቃደ:- አትጠራጠር… ያውም ከጥርስም በላይ … የሰው ጥርስ ቁጥር 32 ነው አይደል ..? ፕሪሚየር ሊጉ ደግሞ 64 ወይም 100 ጥርስ ነው ያለው አትጠራጠር … ጠንካራ የሆነ ቦርድ አለን … መመሪያና ደንቦች አሉን … የውድድርና ስነስርዓት ኮሚቴ ጠንካራ ነው አያልፍህም … በእኛና በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን መሃል ልዩነት የለም ..ከመቼውም ጊዜ በላይ በላይ አብሮ የመስራት ፍላጎቱ አለን…. ምን ትፈልጋለህ ..? 100 ጥርስ ነው ያለን .. ለክለቦቹ ለተጨዋቾቹ ባትዳፈሩን መልካም ነው የምለው ../ሳቅ/ የምንሰማው ጭምጭምታ እውነት ፈጽመው ከተገኙ የተገኙት ላይ ጥርጥር አይኑርህ ርምጃው ይከፋል… አይድኑም አያመልጡም ይሄን አረጋግጥልሃለሁ
ሊግ:- ህጉ የተዘጋጀው በጀት ላጠረባቸው ኢትዮጵያ ቡናና ቅዱስ ጊዮርጊስ ሲባል ነው የሚሉ ወገኖች አሉ…
እርስዎስ ምን ይላሉ..?
ፈቃደ:- ምን ማለት እንደሆነ አላውቅም …እስቲ ስለ ኢትዮጵያ ቡና ላውራህ… አንድም ቀን ኢንሴቲቭ ከመስጠት አቁሞ አያውቅም …ደመወዝ በጊዜው ይከፍላል…. አንድም ቀን ሆቴል ሄዶ ሰርቪሱም ሰውም አልተያዘበትም /ሳቅ/ ይሄ ሁሉ እያለ የምን ወሬ ነው ..? አንዳንድ ክለቦች ቴሌቶን ተደርጎላቸው ነው ያገገሙት… ታዲያ ሁለቱን በእግራቸው የቆሙትን ክለቦች እንዴት ይተቻሉ..? ከመንግስት በጀት አይነኩ መንግስትን አያስቸግሩ .. በራሳቸው በጀት የሚተዳደሩ የረጅም አመት ታሪክና መሰረት ያላቸውን ክለቦች ገንዘብ ተቸግራችሁ እንዴት ይላሉ..? ይሄ ተገቢ አይደለም …. በኔ ጉዳይ ላይ ሌላው እንዴትስ ኮመንት ይሰጣል… ? በከፍተኛ ደረጃ ካሉ አመራሮች ጋር አውርተናል አንድም ቀን ሜዳ ውስጥ ስላለው እግርኳስ አላወራንም ጉዳዩንም አያውቁትም … በቅርቡ አንድ የክለብ አሰልጣኝም ያለ እውቀት የሆነ አስተያየት ሰጥቷል። ኮመንቴ ማድረግ ካለበትም ስብሰባ ላይ የነበረ አካል ብቻ ነው ያልነበረ ያልተሰበሰበ ኮመንት ሲሰጥ ያበላሻል ተገቢም አይደለም ይሄ መታረም አለበት …
ሊግ:– ዝውውር ላይ ደከም አልን ዘንድሮ ቡና ዋጋ የለውም ለሚሉ የርስዎ ምላሽ ምንድነው..?
ፈቃደ:– አንድ ሱቅ ገብተህ ጃኬት አየህና ስለወደድከው ዋጋ ጠየክ ትላንት የተጻፈበት 300 ብር ነው ስለወደድከው መጣህና ነጋዴውን ስትጠይቀው እንደ ወደድከው አውቆ ሂሳቡን 600 ብር ነው ይልሃል ስለፈለከው እሺ አምጣው ትለዋለህ ውደደው እንጂ 10ሺህ ብር ቢልህ ግን አትገዛውም እኛ ጋር የሆነው እንደዚህ ነው 10 ሺህ ስትለኝ ተመሳሳይ የሆነ በ400 ብር የማገኘው ጃኬትኮ እኔ ቤት አለ። እህቴ ጋርም ተመሳሳዩ አለ በነጻ ትሰጠኛለች ለምን ብዬ 10 ሺህ ብር እሺ እልሃለሁ በተቃራኒው እኔ ከወጣሁ በኋላም ለእኔም ከሰጠኧኝ የጃኬት ዋጋ በግማሽ ወርደህ ለሌላ ሰው ከሸጥከው ደግሞ በጣም ያሳዝናል። ያ ደግሞ አንተ ነጋዴ አለመሆንህን ያሳያል።
ሊግ:– ግን መቶ አለቃ ነጋዴ እንደርሱ ያደርጋል።
ፈቃደ:– /ሳቅ/ በፍጹም አያደርግም /ሳቅ በሳቅ/
ሊግ:- ታዲያ በ2017 ለዋንጫ የሚወዳደር ቡድን እንጠብቅ…?
ፈቃደ:– አዎ በደንብ ለምን አይወዳደርም ..? ሁሌ ሰዎችን ተጨዋዋቾችን አሰልጣኞችን አመራሮችን ዝም ብሎ የመውቀስ ባህሪ ያላቸው የመውቀስ ባህሪ አብሯቸው የተወለደ ለክለቡ ሰባራ ሳንቲም የማይሰጡ የፈረደበት ፌስ ቡክ ላይ እንደፈለጉ የሚናገሩ ዋልጌ ደጋፊዎች አሉ ከነርሱ ውጪ ጥረታችንን የሚያዩ የሚያበረታቱ ክፍተት ሲያዩ የሚተቹ አሉ እነሱን አይመለከትም አንድ ምሳሌ ልስጥህ ዘንድሮ ውሉ አልቆ የለቀቀውን ተጨዋች ያስፈረምነው አምና ነው ያኔ ስናመጣቸው ብዙ ሰው ተቃወመ.. ከየትም ሰብስቦ ክለባችንን መጫወቻ አደረገው አሉ አሁንም ጨርሰው ሲወጡ ተቃወሙ ይሄን አናስተናግድም እንደ ቡድን ለጠየከኝ በወጣት የተሞላ ጥሩ ስብስብ ይኖረናል የማቀናጀቱ ስራ የአሰልጣኞቹ ይሆናል። ሁሌ ጥረታችን ሻምፒዮን እንዲሆን ነው ዘንድሮ ዋንጫ ያጣነው በግብ ጠባቂዎቹ ዲፓርትመንት ድክመት ነው ሂዱና ተመልከቱ … አሁንም ቡድኑን ሊያፈርሱ ነው ይላሉ ተተኪ አለ አያምኑንም… ስድብ ትችት ብቻ …
ሊግ:– ኢትዮጵያ ቡና ሲኒየሮቹን ለቅቆ ወጣቶችን ከከፍተኛ ሊግ እያስፈረመ ነው ይሄ ደግሞ ተፎካካሪ አያደርገንም ብለው የሚቃወሙ አሉ ..
ፈቃደ:- ተፎካካሪ እንሆናለን …አይቀርም … በቀጣይ ኤሊት ሆኖ የተለየ አሳማኝ ብቃት ኖሮት ቡናን ፈልጎ ካልመጣ እንደ ፖሊሲ ከፕሪሚየር ሊግ ተጨዋች አናመጣም….. አበቃ…ለዚህም ቆሚ የሆነ መልማይ ቡድን እናቋቁማለን ወጣቶች ላይ እንሰራለን።
ሊግ:– በዚህ መሰል አካሄድ ዋንጫ ማሰብ አይከብድም ..?
ፈቃደ:– ለምን ይከብዳል ..? በነኚሁ ለዋንጫ እንጣወታለን ወጣት ላይ በደንብ ከሰራን አሸናፊ ቡድን ይኖረናል..ለኔ ምሳሌ የሚሆኑት ኤልፓዎች ናቸው… በማስተር ሃጎስ ደስታ ዘመን በወጣቶች የተገነባ ቡድን አየን አንድም የሚታወቅ ተጨዋች አልነበረበትም ግን ሁለት አመት በተከታታይ የፕሪሚየር ሊጉን ዋንጫ አነሱ.. ይሄ ታሪክ ኢትዮጵያ ቡና መድገም ይችላል…
ሊግ:- መቶ አለቃ በኢትዮጵያ ቡና የአመራርነት ቆይታዎ አላሳካሁም ብለው የሚያዝኑበት ነገር የለም ..?
ፈቃደ:– ሁሉንም በአቅምህ ነው … ቢሊየነር የነበረ ድርጅትን ደርግ መጥቶ እናት ድርጅቱን ነጠቀውና አሳጣው ከዚያ በኋላኮ በአብዛኛው ታሪክ የማገገም ስራ ነው የተሰራው በግለሰብም በድርጅትም ስፖንሰርሺፕ እያለ እየጠየቀ ህልውናውን የማቆየት ስራ ነው የተሰራው …ደርግ ባይገፋው እንደ ኢትዮጵያ ቡና ኮርፖሬሽን አይነት ድርጅት ከኋላው ቢኖር ብዙ ዋንጫዎችን መደርደር ይችል ነበር .. ባለፉት አመታት ሳይራብ ክለቡን አቆይተነዋል የሚፈለገውን አሟልተናል የተጨዋች ደመወዝ ምግብ ትራንስፖርት አሟልተናል ማበረታቻ ሰጥተናል ይህን አሟልተን መጥተናል … እንዴት ብለህ አትጠይቀኝ እንጂ በቀጣይ አምስት አመታት ኢትዮጵያ ቡናን የሚያክል የስፖርት ክለብ ኢትዮጵያ ውስጥ አይኖርም ይህን ደግሞ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ታየዋለህ ..
ሊግ:- ጨረስኩ… የመጨረሻ መልዕክት ካሎት ..?
ፈቃደ:– ለሁሉም ክለቦች መናገር እፈልጋለሁ … በጋራ ሆነን የፋይናንስ መመሪያ አውጥተናል…የፋይናንስ መመሪያው ሁሉም ክለብ ከፍተኛ ገንዘብ ከማውጣት ተቆጥበን በዚህ መመሪያ እንመራለን ብለን ያወጣነው ህግ ነው..የክለቦቹ ከፍተኛ በጀት የደመወዝ ክፍያ ነው። ተጨዋቾች አይደጉ አይባልም ቅድሚያ ግን ክለቡ መሆን አለበት ሊፈርሱ ከጫፍ የደረሱ ክለቦችኮ አሉ ክለቦቹ እየፈረሱ ተጨዋቹ ደግሞ ደመወዙን በሚሊየን እያሳደገ መሄዱ ይቃረናል ክለብ ካለ ተጨዋች ይኖራል አዲሱ መመሪያ ክለቦቹና ተጨዋቾቹ በጋራ እንዲያድጉ የሚያደርግ ነው ከዚህ መመሪያ በኋላ በቀጣይ አመት ሁለተኛው መመሪያ ይመጣል በቀጣይ ምን ታስቧል ከተባለ መንግስት 100 ብር ቢሰጥህ 60 ብሩን ለክፍያው ለወጪው ተጠቀምና 40 ብሩን ለእግርኳሱ ልማት አውለው ልንልኮኮ ነው … በ40 ብሩ መለማመድ አለባቸው። ሁሉንም በልቶ መጨረሱ ተገቡ አይደለም ያውም 3 ወራት በደንብ ትበላና 9 ወራቱ ደግሞ የሚበላ የሚላስ የሌላቸው ክለቦች አሉ በዚህ ሁኔታ አንቀጥልም አርቀን ማሰብ አለብን ክለቡን የወደደ በፋይናንስ አስተዳደር ጤነኛ ማድረግ ይጠበቃል ሁለተኛው ክለቦቻችንን ህዝባዊ ማድረግ ብዙ ደጋፊ እንዲኖራቸው ማድረግ ሶስተኛ ደግሞ ክለቦቹ ከአካባቢያቸው ስፖንሰር ማግኘት አለባቸው ..እንዲህ እያልን ክለቦቻችንን ወደ ክለብነት መለወጥ አለብን። ለዚህ ደግሞ በጋራ እንተጋገዝ ማለት እፈልጋለሁ .. አመሰግናለሁ።
ሊግ:- መቶ አለቃ እኔም ከልብ አመሰግናለሁ።